Sunday, September 25, 2011

ፍቅር፤ ከፍቅር እስከ መቃብር


ፍቅር የአየር ንብረት አይደለም፡፡ ሳይተነብዩት መጥቶ፥ ሳይተነብዩት ይሄዳል፡፡ የደምሴ እና የሰላም ፍቅርም እንዲሁ ሳይተነበይ መጥቶ ነው የሄደው:: ሲመጣ፥ ለሁለቱም መጣ፡፡ አካሔዱ ግን እንዳመጣጡ ቀላል አልነበረም፡፡

ደምሴ ቆፍጣና የፍልስፍና መምህር ነው፡፡ ሰላም ደግሞ ቀልቃላ ቢጤ የውበት ባለሙያ፡፡ ነገረ ሥራቸው ሁሉ እሱን ወንዳወንድ እሷን ሴታሴት ያደርጋቸዋል፡፡ የመጀመሪያ ሰሞን ‹‹በፊዚክስ ሕግ ተቃራኒዎች ይሳሳባባሉ›› ይላት ነበር ፍቅራቸውን ሲገልጸው፡፡ ኋላስ?!

ደምሴ እና ሰላም የተዋወቁት የሰው ሠርግ ላይ ነው፡፡ አጋጣሚ ጎን ለጎን አስቀመጣቸው፣ አጋጣሚ እሷን መኪና አሳጣት እና ወደፎቶ ፕሮግራም በእሱ መኪና ሄደች፡፡ ሁሉም በአጋጣሚ ፈጠነ፡፡ ደምሴ ሲያወሩት የሚያወራ፣ ሲዘጉት የሚዘጋ ዓይነት ሰው በመሆኑ ከሰላም ተጫዋችነት ጋር በጊዜው ሰምሮ ነበር፡፡

ሲመሽ ወደ ቤቷ ሸኛት፡፡ መኪና ውስጥ ትንሽ አወጉ፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ ሰላም እባላለሁ›› አለችው፡፡

‹‹ኦው!›› አለ፤ ለካስ እስካሁን ስማቸውን አልተለዋወጡም፡፡

‹‹ደምሴ እባላለሁ፤›› አላት፡፡

‹‹ደምሴ?›› አለችው፡፡ ‹‹አዎ›› አላት፤ የገረማት ትመስላለች፡፡ ለምን እንደገረማት ግን እራሷም አልገባትም፡፡ ምናልባት ጨዋታው እንዲቀጥል ፈልጋ ይሆናል፡፡

‹‹ደምሴ ማለት ደምስሴ ማለት ነው፤›› የፍልስፍና ማብራሪያውን ሳያስበው ማዥጎድጎድ ሊጀምር ነው፡፡

‹‹ኢትዮጵያውያን ምኞቶቻቸውን በልጆቻቸው ማሳካት ይፈልጋሉ፡፡ ምናልባት የኔ ወላጆች አድጌ እንድደመስስላቸው የሚፈልጉት ጠላት ሳይኖራቸው አይቀርም ነበር፡፡ ያለዚያ ደምሴ አይሉኝም ነበር፡፡››

Saturday, May 21, 2011

በድሉን ሰድጄ፥ ሃብታሙን አመጣሁ


በድሉ ‹‹ሰኒ ከዳችኝ›› እያለ ላገኘው ሰው ሁሉ የሚያወራው የቀድሞ ፍቅረኛዬ ነው፡፡ የሚገርመው ሰው ሁሉ ያምነዋል፡፡ ‹‹ድሃ ስለሆንኩ ከዳችኝ›› እያለ ነው የሚያወራው፡፡ ሴት ልጅ ከሃብታም ፍቅረኛዋ ተጣልታ ድሃ ካፈቀረች ‹‹ምን አስነክቷት ነው?›› ይባላል፤ ከድሃው ተጣልታ ሃብታም ስታፈቅር ደግሞ ‹‹በገንዘብ ቀየረችው›› ይላሉ፡፡ ሰው ማውራቱን ላያቆም የኔ ሰውነት በሐፍረት ተሸማቀቀ፡፡

በድሉን በሃብትሽ መተካቴ የሚገርማቸው ሰዎች ሁሉ ሁለቱንም እንደኔ ስለማያውቋቸው አልፈርድባቸውም፡፡ ለዚህ ነው ዛሬ ለናንተ የምነግራችሁ፡፡ ከድሮ ታሪካቸው ብጀመርላችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ በድሉ ወላጆቹ ስሙን የሰጡት በአጋጣሚ እንዳይመስላችሁ፤ ሳይፈለግ በመወለዱ ‹‹በድሉ ይደግ›› ብለው ነው፡፡ እንዳሉትም በድሉ አደገ፡፡ አሁን ጎበዝ ብረት በያጅ ቢሆንም ገቢው ግን እንኳን ሰው ጨምሮበት ለራሱም ከእጅ ወዳፍ ነው፡፡

ሃብታሙ ደግሞ ገና ተፀንሶ እያለ አባቱ አምባሳደር ሆኖ በመሾሙ ለቤተሰቡ ብርቅ ነበር፡፡ አሪፍ ትምህት ቤት ተምሮ በጂኦሎጂ ዲግሪውን ከያዘ በኋላ ከአዲስ አበባ ወጥቶ እንዳይሰራ ሲባል የተከፈተለትን ሰፊ ካፌ እና ሬስቶራንት ያስተዳድራል፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ የማያንቀላፋ ገበያ ያለው ካፌ ብቻ ነው፤ ማን ከአፈር ጋር ይዳረቃል?

እናላችሁ፥ እኔ ሰናይት በድሉን ለገንዘብ ብዬ እንደከዳሁት ለማመን ሁሉም ሰው ይቸኩላል፡፡ ግን አይደለም፡፡ ሃብትሽዬ አንድም ቀን ገንዘብ ሰጥቶኝ አያውቅም፡፡ ታሪኬን ላውራላችሁ እና ራሳችሁ ፍረዱ፡፡

Tuesday, April 19, 2011

የመንግስት ሠራተኛው የፍቅር ቀጠሮ (Version: ከደሞዝ ጭማሪ በኋላ)



የመንግስት ሠራተኛው ከሜላት ጋር ላለመገናኘት የፈለገው የዛን ዕለት እንጂ ከጥር ወር የደሞዝ ጭማሪ በኋላ አይደለም፡፡ ስለዚህ ስልኩን ስላጠፋበትና ቀጠሮው ላይ ላልተገኘበት አሳማኝ ምክንያት እያሰሰ ነው፡፡ “እንዳስፈላጊነቱ አንዱን መግደል ነው” ሐሳቡ ፈገግ አሰኘው፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ትምህርት ቤት እና መሥሪያ ቤት ሲቀር የገደላቸው ዘመድ አዝማዶቹ የመቃብር ቦታ ሳያጣብቡ አይቀሩም፡፡ “እስኪ ማን ሞተ ልበላት?” ብሎ አሰበ፡፡

ሦስት ቀናትን ያለፌስቡክ አሳለፈ፤ አቤት እንዴት ይከብዳል? ሜላትም አልደወለችም፤ ምናልባት በቀጠሮው ሰዓት ስልኩን አጥፍቶ ስለቀረባት አኩርፋው ይሆን? በስንት መከራ እሺ ያስባላትን ቀጠሮ “ድጋሚ እንዴት ነው የሚሆነው?” በመጨረሻ ሁነኛ መላ መጣለት፤ መቼም እናትን ከመግደል ማሳመም ሳይሻል አይቀርም፡፡

የፌስቡክ ግድግዳው ላይ እንዲህ ብሎ ጻፈ፡፡ “የእናቴ ድንገተኛ ሕመም አስደንግጦአችሁ፣ ከአጠገቤ ሳትለዩ የከረማችሁ ጓደኞቼ ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፤ እናቴ አሁን በሙሉ ጤንነት ውስጥ ትገኛለች፡፡” ጓደኞቹ ባልሰሙት አስደንጋጭ ዜና ኮሜንታቸውን አዥጎደጎዱት፤ ለብዙዎቹ በmessage box ማስተካከያ ለመላክ ቢገደድም “ይሁና፤ ሜላትን መልሶ ለማግኘት ሲባል” እያለ ራሱን እያፅናና ነበር፡፡ በመጨረሻ ሜላት “I’m sorry” የሚል comment አሰፈረች፡፡ “ምን ማለቷ ነው? የኔ እናት መታመም አያሳስባትም ማለት ነው? ይቅርታ አታደርግልኝም ማለት ነው?” አዘነባት፡፡