Tuesday, April 19, 2011

የመንግስት ሠራተኛው የፍቅር ቀጠሮ (Version: ከደሞዝ ጭማሪ በኋላ)



የመንግስት ሠራተኛው ከሜላት ጋር ላለመገናኘት የፈለገው የዛን ዕለት እንጂ ከጥር ወር የደሞዝ ጭማሪ በኋላ አይደለም፡፡ ስለዚህ ስልኩን ስላጠፋበትና ቀጠሮው ላይ ላልተገኘበት አሳማኝ ምክንያት እያሰሰ ነው፡፡ “እንዳስፈላጊነቱ አንዱን መግደል ነው” ሐሳቡ ፈገግ አሰኘው፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ትምህርት ቤት እና መሥሪያ ቤት ሲቀር የገደላቸው ዘመድ አዝማዶቹ የመቃብር ቦታ ሳያጣብቡ አይቀሩም፡፡ “እስኪ ማን ሞተ ልበላት?” ብሎ አሰበ፡፡

ሦስት ቀናትን ያለፌስቡክ አሳለፈ፤ አቤት እንዴት ይከብዳል? ሜላትም አልደወለችም፤ ምናልባት በቀጠሮው ሰዓት ስልኩን አጥፍቶ ስለቀረባት አኩርፋው ይሆን? በስንት መከራ እሺ ያስባላትን ቀጠሮ “ድጋሚ እንዴት ነው የሚሆነው?” በመጨረሻ ሁነኛ መላ መጣለት፤ መቼም እናትን ከመግደል ማሳመም ሳይሻል አይቀርም፡፡

የፌስቡክ ግድግዳው ላይ እንዲህ ብሎ ጻፈ፡፡ “የእናቴ ድንገተኛ ሕመም አስደንግጦአችሁ፣ ከአጠገቤ ሳትለዩ የከረማችሁ ጓደኞቼ ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፤ እናቴ አሁን በሙሉ ጤንነት ውስጥ ትገኛለች፡፡” ጓደኞቹ ባልሰሙት አስደንጋጭ ዜና ኮሜንታቸውን አዥጎደጎዱት፤ ለብዙዎቹ በmessage box ማስተካከያ ለመላክ ቢገደድም “ይሁና፤ ሜላትን መልሶ ለማግኘት ሲባል” እያለ ራሱን እያፅናና ነበር፡፡ በመጨረሻ ሜላት “I’m sorry” የሚል comment አሰፈረች፡፡ “ምን ማለቷ ነው? የኔ እናት መታመም አያሳስባትም ማለት ነው? ይቅርታ አታደርግልኝም ማለት ነው?” አዘነባት፡፡