Friday, March 16, 2012

እውነት እና እስር ቤት


“የኔ ውድ! እውን እናትሽን ገድሏል ያሉሽን አምነሽ ተቀበልሻቸው? አዎ! እናትሽን አልወዳቸውም ነበር፤ ግን እኮ እርሳቸውም አይወዱኝም ነበር!

“በእናትሽ ሞት ተጠርጥሬ እስርቤት ከገባሁ ወዲህ ስለእውነት ያለኝ አመለካከት ተቀይሯል፡፡ እውነት የለም! ያለውም ቢሆን ጥቅም የለውም፡፡ ቢኖረውማ እኔን እስር ቤት ሳይሆን የክብር ኒሻን ነበር የሚያሸልመኝ፡፡

የኔ ውድ! አንቺ የኔን ዲስኩር ለመስማት ምንም ዓይነት ፍላጎት እንደማይኖርሽ አውቃለሁ፡፡ ግን አማራጭ የለኝም፡፡ ‹እወድሻለሁ፣ እወድሃለሁ› ተባብለን በፍቅር ከተለያየንበት ከዚያን ቀን ወዲህ ዓይኔን ማየት እንኳን እንዳስጠላሽ አውቃለሁ፤ አልፈርድብሽም፡፡ የናቷን ገዳይ ባልዋን ማየት የምትፈልግ ሴት የታለች?

“ይሄን ደብዳቤ ስጽፍ ተስፋ ያደረግኩት ‹እውነት ነፃ ያወጣኛል› ብዬ አይደለም፡፡ እውነት ነፃ እንደማያወጣኝ እዚሁ እስር ቤት ተምሬያለሁ፡፡ እውነቴ ልክ እንደነፃነቴ በሌሎች እጅ ወድቋል፡፡ ይልቅስ የኔ ውድ! እኔ ተስፋ ያደረግኩት በማህፀንሽ ያለው እውነት እንደሌላው ነገር ሁሉ ውሸት ሆኖ እንዳይቀር ነው፡፡

“ስለዚህ የኔ ውድ! የምጨቀጭቅሽ ስላሳለፍነው ጣፋጭ የፍቅር ዘመን፣ የቤተሰቦቻችንን ቅሬታ ችላ ብለን ስለከፈልነው መስዋዕትነት ወይም በትዳር ያሳለፍናቸው አምስት ዓመታት ተመልሰው ይመጣሉ የሚል ተስፋ ኖሮኝ አይደለም፡፡ እንደሱማ ቢሆን ሌላው ቀርቶ ጭቅጭቃችንም ይናፍቀኛል፡፡ የኔ ውድ! በእኛ እውነትና ውሸት የሁለት ወር ፅንስ ልጃችን ሁለተኛ ሟች እንዳይሆን የመጨረሻ ሙከራ ለማድረግ ነው የኔ ድካም፡፡