Saturday, May 21, 2011

በድሉን ሰድጄ፥ ሃብታሙን አመጣሁ


በድሉ ‹‹ሰኒ ከዳችኝ›› እያለ ላገኘው ሰው ሁሉ የሚያወራው የቀድሞ ፍቅረኛዬ ነው፡፡ የሚገርመው ሰው ሁሉ ያምነዋል፡፡ ‹‹ድሃ ስለሆንኩ ከዳችኝ›› እያለ ነው የሚያወራው፡፡ ሴት ልጅ ከሃብታም ፍቅረኛዋ ተጣልታ ድሃ ካፈቀረች ‹‹ምን አስነክቷት ነው?›› ይባላል፤ ከድሃው ተጣልታ ሃብታም ስታፈቅር ደግሞ ‹‹በገንዘብ ቀየረችው›› ይላሉ፡፡ ሰው ማውራቱን ላያቆም የኔ ሰውነት በሐፍረት ተሸማቀቀ፡፡

በድሉን በሃብትሽ መተካቴ የሚገርማቸው ሰዎች ሁሉ ሁለቱንም እንደኔ ስለማያውቋቸው አልፈርድባቸውም፡፡ ለዚህ ነው ዛሬ ለናንተ የምነግራችሁ፡፡ ከድሮ ታሪካቸው ብጀመርላችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ በድሉ ወላጆቹ ስሙን የሰጡት በአጋጣሚ እንዳይመስላችሁ፤ ሳይፈለግ በመወለዱ ‹‹በድሉ ይደግ›› ብለው ነው፡፡ እንዳሉትም በድሉ አደገ፡፡ አሁን ጎበዝ ብረት በያጅ ቢሆንም ገቢው ግን እንኳን ሰው ጨምሮበት ለራሱም ከእጅ ወዳፍ ነው፡፡

ሃብታሙ ደግሞ ገና ተፀንሶ እያለ አባቱ አምባሳደር ሆኖ በመሾሙ ለቤተሰቡ ብርቅ ነበር፡፡ አሪፍ ትምህት ቤት ተምሮ በጂኦሎጂ ዲግሪውን ከያዘ በኋላ ከአዲስ አበባ ወጥቶ እንዳይሰራ ሲባል የተከፈተለትን ሰፊ ካፌ እና ሬስቶራንት ያስተዳድራል፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ የማያንቀላፋ ገበያ ያለው ካፌ ብቻ ነው፤ ማን ከአፈር ጋር ይዳረቃል?

እናላችሁ፥ እኔ ሰናይት በድሉን ለገንዘብ ብዬ እንደከዳሁት ለማመን ሁሉም ሰው ይቸኩላል፡፡ ግን አይደለም፡፡ ሃብትሽዬ አንድም ቀን ገንዘብ ሰጥቶኝ አያውቅም፡፡ ታሪኬን ላውራላችሁ እና ራሳችሁ ፍረዱ፡፡