Monday, December 4, 2017

ቺምፕያ ሪፐብሊክ

በኬንያና ኡጋንዳ አዋሳኝ ድንበር ላይ ታይቶ የማይታወቅ ነገር ተከሰተ። ቢቢሲ፣ ሲኤንኤን፣ አልጄዚራ የሙሉ ቀን ሰበር ዜናቸው ይኸው ክስተት ሆነ። ፕሬዚደንት ትራምፕ ጉዳዩን አጣርቶ አስቸኳይ እርምጃ የሚወስድ ኮማንድ ፖስት አቋቋሙ። የሲአይኤ ሰው አልባ አውሮጵላኖች በአፍሪካ ሰማይ ላይ ይራወጡ ጀመር። የመላው ዓለም ዓይን ምሥራቅ አፍሪቃ ላይ አፈጠጠ።

ኦክቶበር 20, 2018 በኬንያ እና ኡጋንዳ ድንበር ላይ የሚገኙ የቺምፓንዚ ዝርያዎችን ለማጥናት የተላኩ 15 የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው የናሽናል ጄኦግራፊ አጥኚ ቡድን አባላት ባልታወቁ አካላት ተገደሉ። የእነርሱን ገዳዮች አድመው ለመያዝ የተላኩት የኬንያና የኡጋንዳ የሠለጠኑ ፖሊስ አካላትም በዚያው ቀልጠው ቀሩ። የሲአይኤ የስለላ አውሮጵላኖች ያነሱት ፎቶግራፍ እንደሚያመለክተው ሁሉም ሟቾች  በጦር ተወግተው ነው የሞቱት።

የሰዎቹን አስከሬን ለማምጣት የተላኩት ሄሊኮፕተሮች ከአንዱ በስተቀር እንደጥይት በሚወናጨፉ ግዙፍ ድንጋዮች ተመትተው ወደቁ። የአንዱ ሄሊኮፕተር አብራሪ አስከሬን ለማንሳት በወረወረው መንጠቆ ሰዎቹ ከተገደሉበት ጦር አንዱን ይዞ ተመለሰ። በዓለም የታወቁ ሳይንቲስቶች ጦሩን እንደነጠረ ማዕድን ከበው መረመሩት። የጦሩ ጫፍ በደም ውስጥ በፍጥነት በመሰራጨት ገዳይ የሆነ መርዝ ተቀብቷል። መርዙ ሁለት በምሥራቅ አፍሪካ ሳቫና ብቻ የሚገኙ የዛፍ ቅጠሎችን ቀይጦ በመጨቅጨቅ እንደሚዘጋጅ ለማረጋገጥ ሳይንቲስቶቹ ግዜ አልፈጀባቸውም።

ይህ በእንዲህ እያለ በግዙፍ ድንጋይ ወንጭፍ እየተመቱ ከወደቁት የሲአይኤ ድሮኖች መካከል አንዷ ከወደቀችም በኋላ ተንቀሳቃሽ ምስሎችን መላኳን ቀጥላለች። የተማረከችው ድሮን መንቀሳቀሷን ቀጥላለች። ተንቀሳቃሽ ምስሉ የሚደርሳቸው ሰዎች ድሮኗን የማረኳት አካላት እየተቀባበሉ እየተመለከቷት መሆኑን ለማወቅ ብዙ አልተቸገሩም። ድሮኗ እየተመረመረች ነው። እሷም መረጃ መላኳን አላቋረጠችም። በምትልከው ምስል ውስጥ ከፍተኛ ጫጫታ ይሰማል። የሚያስደነግጠው ግን ሌላ ነው።