Thursday, November 28, 2013

የምን ሙስና?

‹‹እና ምን ላድርግ አጎቴ? አውቶቡሶቹ ከገቡ’ኮ ስድስት ወር አለፋቸው፡፡ መጋዘኑ ውስጥ ቆመው በከረሙ ቁጥር ዋጋቸው እየቀነሰ እንደሚሄድ ዘነጋኸው!››

የገንዘብ ሚኒስትሩ አጎቱ በዝምታ ተዋጡ፡፡

‹‹እስኪ ማታ እንገናኝና እንመካከርበት…››

***

በሳምንቱ ሼባ ሪዞርት የተባለ፣ ገና ግንባታው ያልተጠናቀቀ ሆቴል በአገሪቱ ውስጥ ካሉት አምስት የአውቶቡስ አስመጪዎች አራቱን የአውቶቡስ አስመጪዎች ለጨረታ የዋጋ ሰነድ እንዲያስገቡ ጠየቃቸው፡፡ ይህ በሆነ በሳምንቱ ሼባ ሪዞርት ‹‹የተሻለ አማራጭ በማግኘቱ›› ጨረታውን መሰረዙን ተናገረ፡፡ ሌላ አንድ ሳምንት አለፈ፡፡

የገንዘብ ሚንስቴር ሚኒስትር፣ የአስተዳደር ክፍል ኃላፊዎችን ሰብስበው በነባሮቹ የሠራተኞች ማመላለሻ አውቶቡሶችና፣ የሠራተኞችን ምቾት ስለመጠበቅ አዋሩዋቸው፡፡… አውቶቡሶቹ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲገዙ የመወሰኑ ወሬ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በመሰማቱ ሠራተኞች ተደሰቱ፡፡ ሚኒስትሩ በዚህ መሐል ለሙስና መንገድ እንዳይከፈት በአገሪቱ ካሉት አምስቱም የአውቶቡስ አስመጪዎች የዋጋ ማቅረቢያ በታሸገ ኤንቨሎፕ እንዲያቀርብ አስጠነቀቁ፡፡

***

ከአምስቱም አቅራቢዎች በዝቅተኛ ዋጋ አውቶቡስ ማቅረብ የቻለው ድርጅት አውቶቡሶች አስረክቦ ሒሳብ ተረከበ፡፡ ያኔ ሚኒስትሩ ስልክ ተደወለላቸው፤ ከወንድማቸው ልጅ!

‹‹ሃሎ…›› አሉ ሚኒስትሩ፡፡

‹‹አጎቴ… አመሰግናለሁ፡፡ በዕቅዳችን መሠረት ትርፉን ለሪዞርቱ ግንባታ ማስኬጃ እናውለዋለን፡፡ ቀሪውን ደግሞ ፈቃዱን ልቀይረውና የቢሮ ዕቃ ባስመጣበት ይሻላል…›› ሌላም፣ ሌላም… ‹‹… ለማንኛውም አንተ አስብበት››

አጎት ማሰባቸውን ቀጠሉ፡፡

Friday, October 18, 2013

ነጻ መሆንህ እስኪረጋገጥ ወንጀለኛ ነህ! (አጭር ልቦለድ)



‹‹በእግዚአብሔር ስም እምልላችኋለሁ የማውቀው ነገር የለም…›› አለ እየጮኸ፡፡

‹‹ገልብጡት›› አለ ኮማንደሩ፤ አላመነውም ነበር፡፡

ከግራና ቀኙ ቆመው የነበሩት ሁለቱ ፖሊሶች ገፍትረው በአፍጢሙ ደፉት፡፡ ወለሉ የአፈር ስለነበር ብዙም አልተጎዳም፡፡ እግሮቹ ቋንጃ ላይ ወፈር ያለ ቧንቧ ብረት አስገብተው እግሮቹን የኋልዮሽ በመጎተት በጠፍር መሳይ ገመድ ከወገቡጋ አሰሯቸው፡፡ የቧንቧ ብረቱን ዳርና ዳር ይዘው ሲያነሱት ቁልቁል ተዘቀዘቀ፡፡ አንጠልጥለው ግድግዳው ላይ የተሰኩ ሁለት አግድም ምሰሶዎች ላይ ሰቀሉት፡፡

‹‹አሁንስ አትናገርም?›› አለው ኮማንደሩ፡፡

‹‹ኧረ እኔ ምንም የማውቀ…›› የጀመረውን ሳይጨርስ በፊት አንደኛው ፖሊስ በያዘው ደረቅ ጎማ ጀርባውን አደረቀው፡፡

‹‹እውነቱን ትናገራለህ ወይስ አትናገርም?›› አለው ኮማንደሩ በድጋሚ፤ ከመናገር ይልቅ ዝም ማለት ያዋጣል በማለት ዝም አለ፡፡

‹‹ትናገራለህ፣ አትናገርም›› አለው ኮማንደሩ፤ ዝም አለ!

ሁለቱም ፖሊሶች በደረቅ ጎማቸው ተፈራረቁበት፤ ‹‹እናገራለሁ፣ እናገራለሁ…›› አለ በጩኸት፡፡ ዱላውን አቆሙለት ነገር ግን የሚናገረው ስላልነበረው ዝም አለ፡፡

‹‹ተናገራ፣…›› አለ ኮማንደሩ በብስጭት ጩኸት እያምባረቀ ከጥቂት ደቂቃዎች ዝምታ በኋላ፡፡

‹‹እ…ግ…ዚ…አ…ብ…ሔ…ር…ን… ምንም የማውቀው ነገር የለም፡፡›› አለ የመሐላውን እያንዳንዷን ድምፅ አጥብቆ እየጠራ፡፡ ቁጥሩን ለማያስታውሰው ጊዜ ሁለቱ ፖሊሶች በደረቅ ጎማቸው ጀርባው ላይ ተረባረቡበት፡፡

‹‹አትናገርም፣… ›› አለ ኮማንደሩ፡፡

‹‹ምን ልናገር…? በእግዚአብሔር አታምኑም… ኧረ እባካችሁ…››

‹‹እስከ ጥዋት ድረስ አስብበት… እስክትናገር ድረስ ከዚህ አትወርድም›› ብሎት ኮማንደሩ ክፍሉን ለቆ ወጣ፡፡ ሁለቱ ፖሊሶች እጆቹን በካቴና ጠርንፈው ሲያበቁ ኮማንደሩን ተከትለው ከወጡ በኋላ በሩ በላዩ ላይ ተጠረቀመ፡፡ ቤቱ ዓይን በሚያወጣ ጨለማ ተዋጠ፡፡ እንደዘቀዘቁት ይቆያሉ ብሎ አላመነም ነበር፡፡ ከአሁን አሁን አንዳቸው ተመልሰው ይመጣሉ ብሎ አሰበ፣ ተመኘ፣ ፀለየ - ምንም የተለወጠ ነገር የለም፡፡

Friday, March 16, 2012

እውነት እና እስር ቤት


“የኔ ውድ! እውን እናትሽን ገድሏል ያሉሽን አምነሽ ተቀበልሻቸው? አዎ! እናትሽን አልወዳቸውም ነበር፤ ግን እኮ እርሳቸውም አይወዱኝም ነበር!

“በእናትሽ ሞት ተጠርጥሬ እስርቤት ከገባሁ ወዲህ ስለእውነት ያለኝ አመለካከት ተቀይሯል፡፡ እውነት የለም! ያለውም ቢሆን ጥቅም የለውም፡፡ ቢኖረውማ እኔን እስር ቤት ሳይሆን የክብር ኒሻን ነበር የሚያሸልመኝ፡፡

የኔ ውድ! አንቺ የኔን ዲስኩር ለመስማት ምንም ዓይነት ፍላጎት እንደማይኖርሽ አውቃለሁ፡፡ ግን አማራጭ የለኝም፡፡ ‹እወድሻለሁ፣ እወድሃለሁ› ተባብለን በፍቅር ከተለያየንበት ከዚያን ቀን ወዲህ ዓይኔን ማየት እንኳን እንዳስጠላሽ አውቃለሁ፤ አልፈርድብሽም፡፡ የናቷን ገዳይ ባልዋን ማየት የምትፈልግ ሴት የታለች?

“ይሄን ደብዳቤ ስጽፍ ተስፋ ያደረግኩት ‹እውነት ነፃ ያወጣኛል› ብዬ አይደለም፡፡ እውነት ነፃ እንደማያወጣኝ እዚሁ እስር ቤት ተምሬያለሁ፡፡ እውነቴ ልክ እንደነፃነቴ በሌሎች እጅ ወድቋል፡፡ ይልቅስ የኔ ውድ! እኔ ተስፋ ያደረግኩት በማህፀንሽ ያለው እውነት እንደሌላው ነገር ሁሉ ውሸት ሆኖ እንዳይቀር ነው፡፡

“ስለዚህ የኔ ውድ! የምጨቀጭቅሽ ስላሳለፍነው ጣፋጭ የፍቅር ዘመን፣ የቤተሰቦቻችንን ቅሬታ ችላ ብለን ስለከፈልነው መስዋዕትነት ወይም በትዳር ያሳለፍናቸው አምስት ዓመታት ተመልሰው ይመጣሉ የሚል ተስፋ ኖሮኝ አይደለም፡፡ እንደሱማ ቢሆን ሌላው ቀርቶ ጭቅጭቃችንም ይናፍቀኛል፡፡ የኔ ውድ! በእኛ እውነትና ውሸት የሁለት ወር ፅንስ ልጃችን ሁለተኛ ሟች እንዳይሆን የመጨረሻ ሙከራ ለማድረግ ነው የኔ ድካም፡፡

Sunday, September 25, 2011

ፍቅር፤ ከፍቅር እስከ መቃብር


ፍቅር የአየር ንብረት አይደለም፡፡ ሳይተነብዩት መጥቶ፥ ሳይተነብዩት ይሄዳል፡፡ የደምሴ እና የሰላም ፍቅርም እንዲሁ ሳይተነበይ መጥቶ ነው የሄደው:: ሲመጣ፥ ለሁለቱም መጣ፡፡ አካሔዱ ግን እንዳመጣጡ ቀላል አልነበረም፡፡

ደምሴ ቆፍጣና የፍልስፍና መምህር ነው፡፡ ሰላም ደግሞ ቀልቃላ ቢጤ የውበት ባለሙያ፡፡ ነገረ ሥራቸው ሁሉ እሱን ወንዳወንድ እሷን ሴታሴት ያደርጋቸዋል፡፡ የመጀመሪያ ሰሞን ‹‹በፊዚክስ ሕግ ተቃራኒዎች ይሳሳባባሉ›› ይላት ነበር ፍቅራቸውን ሲገልጸው፡፡ ኋላስ?!

ደምሴ እና ሰላም የተዋወቁት የሰው ሠርግ ላይ ነው፡፡ አጋጣሚ ጎን ለጎን አስቀመጣቸው፣ አጋጣሚ እሷን መኪና አሳጣት እና ወደፎቶ ፕሮግራም በእሱ መኪና ሄደች፡፡ ሁሉም በአጋጣሚ ፈጠነ፡፡ ደምሴ ሲያወሩት የሚያወራ፣ ሲዘጉት የሚዘጋ ዓይነት ሰው በመሆኑ ከሰላም ተጫዋችነት ጋር በጊዜው ሰምሮ ነበር፡፡

ሲመሽ ወደ ቤቷ ሸኛት፡፡ መኪና ውስጥ ትንሽ አወጉ፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ ሰላም እባላለሁ›› አለችው፡፡

‹‹ኦው!›› አለ፤ ለካስ እስካሁን ስማቸውን አልተለዋወጡም፡፡

‹‹ደምሴ እባላለሁ፤›› አላት፡፡

‹‹ደምሴ?›› አለችው፡፡ ‹‹አዎ›› አላት፤ የገረማት ትመስላለች፡፡ ለምን እንደገረማት ግን እራሷም አልገባትም፡፡ ምናልባት ጨዋታው እንዲቀጥል ፈልጋ ይሆናል፡፡

‹‹ደምሴ ማለት ደምስሴ ማለት ነው፤›› የፍልስፍና ማብራሪያውን ሳያስበው ማዥጎድጎድ ሊጀምር ነው፡፡

‹‹ኢትዮጵያውያን ምኞቶቻቸውን በልጆቻቸው ማሳካት ይፈልጋሉ፡፡ ምናልባት የኔ ወላጆች አድጌ እንድደመስስላቸው የሚፈልጉት ጠላት ሳይኖራቸው አይቀርም ነበር፡፡ ያለዚያ ደምሴ አይሉኝም ነበር፡፡››

Saturday, May 21, 2011

በድሉን ሰድጄ፥ ሃብታሙን አመጣሁ


በድሉ ‹‹ሰኒ ከዳችኝ›› እያለ ላገኘው ሰው ሁሉ የሚያወራው የቀድሞ ፍቅረኛዬ ነው፡፡ የሚገርመው ሰው ሁሉ ያምነዋል፡፡ ‹‹ድሃ ስለሆንኩ ከዳችኝ›› እያለ ነው የሚያወራው፡፡ ሴት ልጅ ከሃብታም ፍቅረኛዋ ተጣልታ ድሃ ካፈቀረች ‹‹ምን አስነክቷት ነው?›› ይባላል፤ ከድሃው ተጣልታ ሃብታም ስታፈቅር ደግሞ ‹‹በገንዘብ ቀየረችው›› ይላሉ፡፡ ሰው ማውራቱን ላያቆም የኔ ሰውነት በሐፍረት ተሸማቀቀ፡፡

በድሉን በሃብትሽ መተካቴ የሚገርማቸው ሰዎች ሁሉ ሁለቱንም እንደኔ ስለማያውቋቸው አልፈርድባቸውም፡፡ ለዚህ ነው ዛሬ ለናንተ የምነግራችሁ፡፡ ከድሮ ታሪካቸው ብጀመርላችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ በድሉ ወላጆቹ ስሙን የሰጡት በአጋጣሚ እንዳይመስላችሁ፤ ሳይፈለግ በመወለዱ ‹‹በድሉ ይደግ›› ብለው ነው፡፡ እንዳሉትም በድሉ አደገ፡፡ አሁን ጎበዝ ብረት በያጅ ቢሆንም ገቢው ግን እንኳን ሰው ጨምሮበት ለራሱም ከእጅ ወዳፍ ነው፡፡

ሃብታሙ ደግሞ ገና ተፀንሶ እያለ አባቱ አምባሳደር ሆኖ በመሾሙ ለቤተሰቡ ብርቅ ነበር፡፡ አሪፍ ትምህት ቤት ተምሮ በጂኦሎጂ ዲግሪውን ከያዘ በኋላ ከአዲስ አበባ ወጥቶ እንዳይሰራ ሲባል የተከፈተለትን ሰፊ ካፌ እና ሬስቶራንት ያስተዳድራል፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ የማያንቀላፋ ገበያ ያለው ካፌ ብቻ ነው፤ ማን ከአፈር ጋር ይዳረቃል?

እናላችሁ፥ እኔ ሰናይት በድሉን ለገንዘብ ብዬ እንደከዳሁት ለማመን ሁሉም ሰው ይቸኩላል፡፡ ግን አይደለም፡፡ ሃብትሽዬ አንድም ቀን ገንዘብ ሰጥቶኝ አያውቅም፡፡ ታሪኬን ላውራላችሁ እና ራሳችሁ ፍረዱ፡፡

Tuesday, April 19, 2011

የመንግስት ሠራተኛው የፍቅር ቀጠሮ (Version: ከደሞዝ ጭማሪ በኋላ)



የመንግስት ሠራተኛው ከሜላት ጋር ላለመገናኘት የፈለገው የዛን ዕለት እንጂ ከጥር ወር የደሞዝ ጭማሪ በኋላ አይደለም፡፡ ስለዚህ ስልኩን ስላጠፋበትና ቀጠሮው ላይ ላልተገኘበት አሳማኝ ምክንያት እያሰሰ ነው፡፡ “እንዳስፈላጊነቱ አንዱን መግደል ነው” ሐሳቡ ፈገግ አሰኘው፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ትምህርት ቤት እና መሥሪያ ቤት ሲቀር የገደላቸው ዘመድ አዝማዶቹ የመቃብር ቦታ ሳያጣብቡ አይቀሩም፡፡ “እስኪ ማን ሞተ ልበላት?” ብሎ አሰበ፡፡

ሦስት ቀናትን ያለፌስቡክ አሳለፈ፤ አቤት እንዴት ይከብዳል? ሜላትም አልደወለችም፤ ምናልባት በቀጠሮው ሰዓት ስልኩን አጥፍቶ ስለቀረባት አኩርፋው ይሆን? በስንት መከራ እሺ ያስባላትን ቀጠሮ “ድጋሚ እንዴት ነው የሚሆነው?” በመጨረሻ ሁነኛ መላ መጣለት፤ መቼም እናትን ከመግደል ማሳመም ሳይሻል አይቀርም፡፡

የፌስቡክ ግድግዳው ላይ እንዲህ ብሎ ጻፈ፡፡ “የእናቴ ድንገተኛ ሕመም አስደንግጦአችሁ፣ ከአጠገቤ ሳትለዩ የከረማችሁ ጓደኞቼ ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፤ እናቴ አሁን በሙሉ ጤንነት ውስጥ ትገኛለች፡፡” ጓደኞቹ ባልሰሙት አስደንጋጭ ዜና ኮሜንታቸውን አዥጎደጎዱት፤ ለብዙዎቹ በmessage box ማስተካከያ ለመላክ ቢገደድም “ይሁና፤ ሜላትን መልሶ ለማግኘት ሲባል” እያለ ራሱን እያፅናና ነበር፡፡ በመጨረሻ ሜላት “I’m sorry” የሚል comment አሰፈረች፡፡ “ምን ማለቷ ነው? የኔ እናት መታመም አያሳስባትም ማለት ነው? ይቅርታ አታደርግልኝም ማለት ነው?” አዘነባት፡፡

Monday, December 6, 2010

የመንግስት ሠራተኛው የፍቅር ቀጠሮ (የdating እንጉርጉሮ)


ዕለቱ ሕዳር 27 ነው፤ የደሞዝ ቀን፡፡ ኪሱ በመቶ ብሮች ታጭቋል፡፡ ማታ የራት ግብዣ አለበት፡፡ የራት ግብዣው አቅራቢ እሱ ነው፤ ተጋባዧ ሜላት፡፡ ለዚህ የራት ግብዣ ብዙ ተዘጋጅቷል፣ በጣም ጓጉቷል፣ እንቅልፍ አጥቷል - በአራት ነጥብ ጉዳዩን ለማሳጠር ያክል የማይሆነውን ሆኗል፡፡

ሜላትን የተዋወቃት በፌስቡክ ነው፡፡ የጓደኞቹ ጓደኛ ፎቶ ላይ ‘Tag’ ተደርጋ አያት፡፡ ሒደቱ ቀላል ነበር፡፡ በመጀመሪያ ፎቶዋን ወደደው፡፡ ከዚያ ‘ፕሮፋይሏን’ ጎበኘ እና ወደደላት፤ በተለይ ‘Single’ መሆኗ ተመቸው፡፡ ለፌስቡክ ጓደኝነት ጠየቃት ተቀበለችው፡፡ ፎቶዎቿን በሙሉ አየ - በቀኝም፣ በግራም፣ በፊትለፊትም፣ በኋላም የተነሳቻቸው ፎቶዎቿ ያምራሉ፡፡ ለፌስቡክ ተራ ጓደኝነት ያንስባታል ብሎ አስቦ ለሌላ ነገር አጫት፡፡ ያንን ሌላ ነገር ሳይነግራት ‘Chat’ ላይ እየጠበቀ ስትገባ ያዋራት ጀመር፡፡ ለነገሩ እሷም ‘easy going’ መሆኗ ተመችቶታል፤ አስፈርቶታልም፡፡ ‘easy going’ መሆኗ ለእሱ ብቻ ካልሆነስ? ደግሞም አይሆንም፡፡

እሱ የመንግስት ሰራተኛ ነው፡፡ 1,600 ብር ተከፋይ የወር ደሞዝተኛ፡፡ ለነገሩ ከዚህችው ላይ ታክስ፣ የጡረታ አበል ምናምን ሲቆራረጥ ከ1,400 ብር በላይ ጥቂት አሥር ብሮች ናቸው የሚተርፉት፡፡ ታክስ የሚባል ነገር ያበሳጨዋል፡፡ “ይቺም ገቢ ሁና በገቢ ታክስ እና በቫት ተቀነጣጥባ ታልቃለች” እያለ ያማርራል፡፡ ምናልባት ብዙ ከተወራለት የጥር ወር ደሞዝ ጭማሪ በኋላ ተስፋ ሰንቋል - በደሞዙ ማነስ ላይማረር፡፡ ስንት ቢጨመርለት እንደማይማረር ግን አስልቶ አያውቅም፣ ማስላትም አይፈልግም፡፡